አቶ አብርሃም አለኸኝ፣ በሚኒስትር ደረጃ የዲሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ አማካሪ ሥልጣናቸውን ለቅቀዋል
Edited by : addiskignit@gmail.com -2/8/2023
ሃይማኖት ብቻ !!! ፖለቲካና ፖለቲከኛ ባልተገናኘበት የፖለቲካ ባህል ውስጥ ፖለቲከኛ መሆን ትርፉ ስቃይ ብቻ ነው። የኔ በምትለው ፖለቲካ ውስጥ የእነሱ የሆነውን ትጨፈልቃለሁ። በጥቅምህ የመጡ ከመሰለህ የያዙትን አጀንዳ ሁሉ ለማስጣል ራስህን ብቸኛ ቅዱስ ታደርጋለህ። የአለም ፖለቲካ ጠባይ ይኸ ነው። በኢትዮጵያ ሰማይ ስር በጠላትነት መፈራረጅን ሊያስቆም የሚችል ፖለቲካም ሆነ ፖለቲከኛ የለም። ጥላቻን መሰረት ያደረገ ፖለቲካ ይቅርታንና ርህራሄን የሚያውቅ ፖለቲከኛ ሊኖረው አይችልም። በጥላቻ መቃብር ላይ ራሱን መስዋዕት ማድረግ የማይችል ፖለቲከኛም የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ቁስል የመፈወስ ጉልበት አይኖረውም። የአገሪቷ ችግር ይኸ ይመስለኛል። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ አሁናዊ አደጋ ዛሬ የተጀመረ ሳይሆን አስርተ አመታትን የተሻገረ ጥላቻ ወለድ ውጥን ነው። ዛሬ የተመለከትነው ውጤቱን ነው። አገሪቷ ተንገዳግዳ እስክትወድቅ ድረስ ነገም ሌላ መልክ ይዞ ይቀጥላል። ሃይማኖትም ሆነ ምግባር የሌለው ትውልድ የመፍጠር ሁሉ አቀፍ ፕሮጀክትም ነው። ጠንካራ አገሮች የተፈረካከሱበትና ለሩስያና ለዩክሬን ወቅታዊ መካረር ስረምክንያት የሆነውም ይኸ ሀቅ ነው። የጋራ ጥቅምን ሰክኖ ከማየት ይልቅ የኔ ብቻ የሚል ባዕድ ፍላጎት። መፍትሄው ከፖለቲካና ከፖለቲከኞች ፈቀቅ ብሎ (ርዕዮተ ዓለማዊ ግጭት ስለሚጫናቸው ቤተክርስቲያኗንም ሆነ ህዝበ ክርስቲያኑን ያደናግሩታል ብየ ስለምሰጋና የትችትን በር ለመዝጋት ስለሚጠቅም) የተጀመረውን አንድነት አጠናክሮ መቀጠል፤ ሰክኖና ተደማምጦ ልባዊ ምክክር ማድረግ፤ ከቤተክርስቲያኗ ዋኖች ጋር ተመካክሮ ዘላቂ መፍትሄ ማበጀት ያስፈልጋል ። በምድረ ኢትዮጵያ የምትገኘዋን አሐቲ ቅድስት ቤተክርስቲያን በእርግጥም የአገር ፈርጥ ማድረግ ይገባል። አጀንዳው ሃይማኖት ብቻ ሲሆን ነው በዕኩይ ፖለቲከኞች ከመጠለፍ አደጋ ተጠብቆ ማሸነፍ የሚቻለው። ኦርቶዶክስ አገር ናት በሚል ጥቅል ሀሳብ ከመታጠር ወጥቶ ጉዳዩን አምልቶና አስፍቶ መረዳትና ማስረዳትም ይገባል። አዎ ኦርቶዶክስ አገር ናት። ታላላቆቸ ቆነፀልከው እንዳይሉኝ እንጂ:- በየጊዜው የተነሱ ፖለቲከኞች ወዲያና ወዲህ እያላጉ ሌላ ቀለም እንዲሰጣት አደረጉ እንጂ የእስልምናን፣ የካቶሊክን፣ የፕሮቴስታንትንና የአይሁድን እምነት በጨዋ ባህልና በትህትና ተቀብላ ያስተናገደች፣ በፍትህ ርቱዕ የምታምን፣ የብዝሀነት መሰረትና ስንዱ እመቤት ናት። እንደአለመታደል ሆኖ ቤተክርስቲያኗን ለመክሰስና ለመውቀስ ሲፈለግ "ቀዳሽና አንጋሽ" በሚል ምፀት ይሞግቷታል። በተቃራኒው በዚህ ሙሉ የስልጣን ክብር በነበረችበት ዘመን ለብዝሀነት መከበር የነበራትን አበርክቶ በደምሳሳው እናልፈዋለን። የዴሞክራሲ ፍልስፍና በውል በማይታወቅበት በዚያ ዘመን የመንግስት ድርሻ ስላለኝ እኔ ብቻ በሚል ጭፍን ብሂል አልታጠረችም። ጥንታዊ መንግስታት በየዘመናቸው ለሚፈጥሩት የህልውና ስጋት ቤተክርስቲያኗን ተጠያቂ ማድረግ የፈጠረው ጥላቻ አምርረው በሚጠሏት ወገኖች በኩል ዱላ እንዲበዛባት አድርጓል። የቤተክርስቲያኗን መለያዎች ሁሉ ብንመለከት መለኮታዊ እንጂ ስጋዊ አይደለም። ስለአገር መሪዎች መፀለይ የቤተክርስቲያኗ ርቱዕ ግብረገብ መገለጫ እንጂ ሌላ ትርጉም የሚያሰጥ ሊሆን አይችልም። እነዚህንና መሰል ጉዳዮችን በመሰንጠቅ ልጆቿን መከፋፈል ያስተዛዝብ ካልሆነ በስተቀር የቤተክርስቲያኗን አገርነት አያጎድለውም። ቤተክርስቲያኗ ከአስራ ምዕት ዘለግ ባለው ታሪኳ ያቀፈቻቸው ምዕመናንና ምዕመናት ከአንድ ወገን ብቻ የተቀዱ ይመስል የፅርፈት ናዳ ማግተልተል ነውር ነው። ትክክል አይደለም እንጂ ትክክል ነው ቢባል እንኳ አሁን ላለንበት ሁኔታ የሚጠቅም እንጥፍጣፊ ፋይዳ የለውም። ሶርያዊ፣ ግብፃዊ፣ አርመናዊ፣ ሊቢያዊ፣ ቱርካዊ ፣ ግሪካዊ፣ ሮማዊ....አበውና እመው ተቀብላ በረከታቸውን ያገኘችና በቃላቸውና በህይወታቸው ከሚፈሰው የትምህርታቸው ጅረት የተደራጀችንና የፀናችን ቤተክርስቲያን የሆነ አውራጃ አክስዮን አድርጎ መፈረጅ "በሬ ሆይ በሬ ሆይ ሳሩን አየህና ገደሉን ሳታይ" አይነት መጤ ስሁት ትርክት ነው። ቀለም በጥብጣ፣ ብራና ዳምጣ፣ ብዕር ቀርፃ፣ ቋንቋን ከእነፊደሉ፣ የዘመን አቆጣጠር ፍልስፍናን ከእነቀመሩ ሰንዳ ከፍትሐነገስት እስከ ዘመናዊ ህገመንግስት አዘጋጅታ ስርአተ መንግስትን ላፀናችና የታሪክ መዛግብት ለሆነች አሀቲ ቤተክርስቲያን ፅርፈት አይገባትም። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያንን ለሁሉም እምነቶች አክብሮት እንዳላት በብዙ መለኪያዎች ማስረዳት ይቻላል። ለዚህ ነው ኦርቶዶክስ አገር ናት ይሚባለው። የጥላቻ ታሪክ መንስኤው የፖለቲከኞች እንጂ የቤተክርስቲያኗ አይደለም። አንድ አንድ በቤተክርስቲያኗ ስም የተነሱ ፀሀፍት ሆን ብለውና በቸልተኝነት የገደፉትንና የፀረፉትን ስህተት በመጥቀስ ቤተክርስቲያኗን አውራጃዊና ዘውጋዊ ካባ በማልበስ ማጠየም የክፉዎች ሴራ እንጂ ትክክለኛ መልኳ አይደለም። ከቤተክርስቲያን የስዕል ጥበብ ታሪክ ጋር በማያያዝ እገሌ ለሚባለው ንጉሰ ነገስት ታደላለች፣ እንዲወደስ ታደርጋለች የሚለው ክስ የወቅቱን ባህላዊ መስተጋብር (the cultural effect of state society relationship) በተዛባ መንገድ በመገንዘብ የሚመጣ ስሁት ብያኔ ነው። ይህንን ማንሳት ያስፈለገው ለአሁናዊው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያንና አገሪቷ ላለችበት ፖለቲካዊ ምስቅልቅል ስረ ምክንያት የሆነውን የተቀናጀ ፖለቲካዊ ሴራ ለመጠቆም ነው። ፖለቲካ የቤተክርስቲያኗ ካንሰር ነው የምለው በምክንያት ነው። ከቤተክርስቲያኗ መሰረታዊ እውነት በተቃርኖ የተሰለፉት ፖለቲከኞች ደግሞ የካንሰሩ መንስኤ ናቸው። አሁን ላይ ቤተክርስቲያኗን እየናጣት ያለው ግራና ቀኝ የተሰለፈ ፍፁም ገለልተኛ ያልሆነ የፖለቲካ ጨዋታ ነው። አገር የማፍረስ የቆየ ዕቅድ ያላቸው ፖለቲከኞች የአገር ምልክት የሆነችውን ቤተክርስቲያን በመከፋፈል ጀምረውታል። ለቤተክርስቲያኗ የወገኑ የሚመስሉ ስውር ፖለቲከኞችም ከጀርባ ሆነው የቤተክርስቲያኗ አላማ ባልሆነ የትግል ስልት (አግላይና ከፋፋይ) መንፈሳዊ ቀለሟን ሲደልዙ ይስተዋላሉ። ከችግሩ ፊት የሚታዩት አካላት ግን ህጋዊው፣ መንፈሳዊውና ሰማያዊው ሲኖዶስና ህገወጥ በሚል የተጠቀሱት የእምነት አባቶች ናቸው። የቤክርስቲያኗ ልጆች ይህንን ስውር ደባ በውል የተረዱት አይመስልም። እነዚህ የእፉኝት ፖለቲካ አቀንቃኞች ቤተክርስቲያንን የመሰንጠቅ ግባቸውን ካሳኩ በኋላ በሁሉም የኢትዮጵያ አውራጃዎች ለሚገኙ ምዕመናንና ምዕመናት የሚያተርፉለት ነገር ቢኖር ለቅሶና ዋይታ ጥርስ ማፋጨት ብቻ ነው። ከፖለቲካም ሆነ ከፖለቲከኞች ጥድፍያና ትንቅንቅ ፈቀቅ ብለን፣ ለመንፈሳዊና ሰማያዊ ዜግነት ያደላ ወይም የወገነ ስነልቦና ገንዘብ እናድርግ። በባህርይ ክርስቶሳዊት የሆነችዋን ቤተክርስቲያንን እናስብ። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያንን በማጎሳቆል ወርቅ የሚጨብጡ የሚመስላቸው ስውር እጆች በተለይም የአገሬ ሰዎች አውራ እያጠፋችሁ መሆኑን ተረዱት። አውራውን ማጥፋት መንጋውን መበተን ነው። አንድ ቀን አውራ ሊያስፈልጋችሁ እንደሚችል ማሰብ ይጠቅማችኋል።
test