ጥላ- ሶስና አሸናፊ
Edited by : sosina ashenafi -8/19/2023
እታለም ሠላሣ ስምንት አመት እንደሞላት ማመን አትፈልግም። " እኔ እንደሁ ከህፃንነት ድርጊቴ አልወጣሁም። ዕድሜዬ ቁጥሩ ቢጨምር ምን ዋጋ አለው" ትላለች ከእንቅልፏ ስትነቃ የሌሊት ልብሷን አልፎ ፍራሽዋን ያራሠ ሽንቷን እየተጠየፈች። የዛሬው ግን ልዩ ነው። ለወሬም አይመች፣ ስትጠነቀቅለት የኖረችውን የብቻ ሚስጥሯን የብቻ ነውሯን እንቅልፍ ጥሏት ገሀድ ወጣባት። ጭልጥ ካለ እንቅልፏ ድንገት ባነነች። ከዚያም ጭኗ መሀል ያለው ሙቀት ተሰማት። በእጇ ዳበሠችው። ፒጃማዋ ርሷል። ቀስ ብላ የአሠፋን ፒጃማ ነካካችው የሱም ርሷል። ደነገጠች። ተጠንቅቃ ከተኛችበት በመሣብ ቁጭ አለችና መካከለኛ ስፋት ያለውን ሮዝ ቀለም የተቀባ መኝታ ቤት በትኩረት ደጋግማ አየችው። የራስጌ መብራቱ አልጠፋም። አይታቸው እንደማታውቅ ሁሉ የቤቱን እቃዎች አማተረች። ሰፊ ቁምሳጥን የሸሚዝ ማስቀመጫ ሳጥን ግድግዳውን ተደግፈው በተለያዩ አቅጣጫዎች ቆመዋል። የእጅ መታጠቢያ ላስቲክ ደግሞ ውሀ ተሞልቶ ተቀምጧል። እንደገና አንድ ሜትር ከሀምሳው አልጋ ላይ አፈጠጠች። ሮዝ አልጋ ልብሱንና ቀይ ብርድልብሱን በየተራ ዳበሰቻቸው። ነጩን አንሶላ በእግሯ እንደመዳበስ እያደረገች አሸችው። በአንሶላው ላይ የሚታየውን እርጥበት ማመን አቃታት። እናም ማልቀስ ጀመረች። አሰፋ የሲቃ ድምጿን ሲሰማ ደንግጦ ተነሳና " እታል . . .እታል ችግር አለ?" አላት ረዘም ያለ ፊቷን እና ረጅም የተጠቀለለ ፀጉሯን በየተራ እየዳሠሠ። ትልልቅ አይኖቹን ላለማየት እየታገለች ሰልካካ አፍንጫውንና ጠባብ ከንፈሮቹን ሳታስበው በእጇ ዳበሠችው። እሱም ፒጃማውን አርሶ ወደ ሰውነቱ የሚያልፈውን ቅዝቃዜ ለማጣራት ብርድልብሱን ገለጠው። ሁለም ርሷል። ደነገጠ:: ሊመለጥ ያለ ፀጉሩን እያሸ ለመናገር ሲል ቃላቶቹ ጠፉበት። "ሳላውቅ ነው::" አለች እያለቀሰች አሰፋ ገባው። "አይዞሽ ችግር የለውም። ያለነው ቤታችን ያየሁት እኔ ብቻ አትረበሺ ። እኔ ባልሽ፣ ወንድምሽ፣ ጓደኛሽ አይደለሁም? " አላት ። እቅፉ ውስጥ እንዳለች ግንባሯን ደጋግሞ እየሳመ። በልቡ ደግሞ ሌላ ነገር አሰበ። "ምን አልባት. . . " የጀመረውን አልጨረሠም። . . . https://youtu.be/4V-MJgnKhYo
test