የሥነ ጽሑፍ ሳሎን እና ሂሩት ካፌ ከአንጋፋውአርቲስት አበበ ባልቻ ጋር ሎሬት ጸጋዬ ገብረመድሕንን ይዘክራሉ

የሥነ ጽሑፍ ሳሎን ከሂሩት ካፌ ጋር በመተባበር ታላቁን ኢትዮጵያዊ ባለቅኔና ጸሐፌ ተውኔት ሎሬት ጸጋዬ ገብረመድሕንን የሚዘክር የሥነ ጽሑፍና የኪነጥበብ ዝግጅት ነሐሴ ወር ላይ ያካሂዳሉ።
ዝግጅቱ ነሐሴ 11 ቀን 2018 ዓ.ም. August 11, 2026 ከምሽቱ 6፡00 ጀምሮ በቶሮንቶ 2050 Danforth Avenue በሚገኘው ሂሩት ካፌ ይካሄዳል። በዝግጅቱም የሎሬት ጸጋዬ ሕይወት፣ ሥራዎችና ለኢትዮጵያ ሥነ ጽሑፍና ቲያትር ያበረከቱት ዘላቂ አስተዋጽዖ ይዘከራል።
በዝግጅቱ ላይ ከሎሬት ጸጋዬ ጋር በቅርበት የሠራውና በበርካታ የሥራዎቹ መድረክ ላይ የተወነው አንጋፋው ተዋናይ፣ ፕሮዲዩሰርና የሕግ ባለሙያ አበበ ባልቻ ይገኛል። አበበ ባልቻ ከሎሬት ጸጋዬ ሥራዎች መካከል በተለይም “ኦቴሎ”ን ጨምሮ በበርካታ የተውኔት ሥራዎች ላይ በመተወን ከባለቅኔው ጋር በቀጥታ ከሰሩ ከያኒያን መካከል ዋነኛው ነው።
የሥነ ጽሑፍ ሳሎን በኢትዮጵያዊያን
ደራሲያን፣ ገጣሚያን፣ ጸሐፌ ተውኔቶችና የሥነ ጽሑፍ አድናቂያን መካከል የሥነ ጽሑፍ ውይይትና ልውውጥን ለማጠናከር በዋትስአፕ የተቋቋመ ማኅበረሰብ ሲሆን፣ ባለፉት ሁለት ዓመታት በመቶዎች የሚቆጠሩ የሥነ ጽሑፍ ባለሙያዎችንና አፍቃሪያንን አገናኝቷል። የሳሎኑ መሥራቾችም ፀሐፊና ጋዜጠኞቹ ሶስና አሸናፊ እና ገዛኸኝ መኮንን ናቸው።
የሎሬት ጸጋዬን ሕይወትና ሥራ በተወለዱበት ወር ለመዘከር ከአበበ ባልቻ ጋር የታቀደው ይህ ዝግጅት ባለፈው ዓመት በሁኔታዎች አለመመቸት
ምክንያት ሳይካሄድ ቀርቶ ነበር። በዚህ ዓመት ግን አበበ ባልቻ ዳግም ቶሮንቶ በመገኘቱ ዝግጅቱ ተዘጋጅቷል።
የሥነ ጽሑፍና የኪነጥበብ ወዳጆች ሁሉ ነሐሴ 11 ቀን 2018 ዓ.ም. ከምሽቱ 6፡00 ጀምሮ በሂሩት ካፌ በመገኘት ታላቁን ባለቅኔና ጸሐፌ ተውኔት ሎሬት ጸጋዬ ገብረመድሕንን አብረው እንዲዘክሩ ጥሪ ቀርቧል።